21/11/2025
የማር-በርግ ቫይረስ ከሌሎች ቫይረሶች አኳያ የሞት ምጣኔው ከፍተኛ ነዉ ተባለ
📌በቫይረሱ ምክንያት ህይወታቸዉን ያጡ ሰዎች አስክሬን ለቤተሰብ አይሰጥም
| በቅርቡ በኢትዮጵያ የተገኘዉ የማር-በርግ ቫይረስን አስመልክቶ በዛሬው እለት የጤና ሚኒስቴር ለመገናኛ ብዙሃን ስልጠና ሰጥቷል፡፡
ቫይረሱ በሞት ከተለየ ሰው የመተላለፍ እድሉ ከፍተኛ በመሆኑም መቃብር ስፍራ ላይም ጥንቃቄን ይፈልጋልም ነው የተባለው፡፡
በመድረኩም ከጤና ሚኒስቴር የተወከሉ እና በዘርፉ ልምድ ያላቸው የህክምና ባለሙያዎችም ተሳትፈዋል፡፡ በመድረኩ ከተነሱ ሀሳቦች መካከል ማር-በርግ ከሌሎች ቫይረሶች አንፃር የሞት ምጣኔው ከ 18 - 88 በመቶ ያህል እንደሆነም ተጠቅሷል።
ቫይረሱ በቀጥታ እንደ የለሊት ወፍ ካሉ አዕዋፋት ጋር በሚኖር ንክኪ የሚፈጠር መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ በሌላ በኩል ቫይረሱ በሞት ከተለየ ሰው የመተላለፍ እድሉ ከፍተኛ በመሆኑም መቃብር ስፍራ ላይም ልዩ ጥንቃቄን የሚፈልግም ነው ተብሏል።
ለህክምናው የሚያስፈልጉ ግብዐቶች ወጪያቸው ከፍተኛ ስለመሆኑ የተገለፀ ሲሆን ድንገተኛ ትኩሳት፣ድካም፣የምግብ ፍላጎት ማነስ እና ሰውነት የመድማት ሁኔታዎች ከምልክቶቹ መካከል ተጠቃሽ ናቸዉ፡፡
ቫይረሱ ከ2-21 ቀን የመቆየት እድል እንዳለው የተገለፀ ሲሆን በሳይንስ የተረጋገጠ ህክምናም ሆነ መድሃኒት የለዉም ተብሏል፡፡
በቫይረሱ ምክንያት ህይወታቸዉን ያጡ ሰዎች አስክሬን ለቤተሰብ እንደማይሰጥ ምክንያቱ ደግሞ የመተላለፍ እድሉ ከፍተኛ በመሆኑ እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡
በሌላ በኩል ቫይረሱ በወንድ የዘር ፈሳሽ ውስጥ ለአንድ አመት ጊዜ የሚቆይ በመሆኑ ፥ ከህመሙ ያገገሙ ሰዎች ልቅ የሆነ የግብረስጋ ግንኙነት ከማድረግ መቆጠብ አለባቸው ተብሏል፡፡
ቫይረሱ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጅንካ ከተማ የተከሰተ ሲሆን በቫይረሱ እስካሁን 33 የላብራቶሪ ምርመራዎችን እንደተደረጉ የጤና ሚኒስቴር መረጀ ያመላክታል ያለው መናኸሪያ ኤፍ ኤም ነው፡፡