30/08/2025
390ሺህ ብር በላይ የተፈፅመ የማጭበርበር ታሪክ. . . (እውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተ)
ከዚህ በታች የምናጋራችሁ ከ390ሺህ ብር በላይ ስለተጭበረበረች የባንካችን ደንበኛ ታሪክ ይሆናል. . .
ወ/ሪት ሄለን ተሾመ (ስም የተቀየረ) በአንድ የመንግስት መስሪያ ቤት ውስጥ በአካውንቲንግ ሙያ ተቀጥራ እያገለገለች የምትገኝ ወጣት ሴት ናት። ወ/ሪት ሄለን በዚህ በምታገኘው ደሞዝ ህይወቱን ትመራለች። ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በመጣው የኑሮ ውድነት እና መሰረታዊ ፍላጎቶቿን ለማሟላት፣ በአንድ ገቢ ላይ ብቻ ተንጠልጥሎ የእሷን እና የቤተሰቧን ህይወት ማሻሻል ከባድ መሆኑን በመገንዘብ ተጨማሪ የኦንላይን (online) ስራዎችን መፈለግ ከጀመረች ሰነባብታለች።
ከእለታት አንድ ቀን ይህ ውጥኗ ተሳክቶ በፌስቡክ ላይ ያየችው ማስታወቂያ ቀልቧን ይስበዋል። ይዘቱም በፎሬክስ ንግድ ላይ ለመሰማራት ከፈለጉ የቴሌግራም ቻናላችንን ይቀላቀሉ የሚል ነበር። ወ/ሪት ሄለንም ፌስቡክ ላይ የተቀመጠውን ሊንክ በመጫን ቴሌግራም ቻናሉን ተቀላቀለች።
ይህ ቴሌግራም ቻናል ከ አርባ ሶስት ሺህ በላይ ሰዎች ስብስክራብ ያረጉት ሲሆን ሰዎች ኢንቨስት አድርገው ትርፋማ እንደሆኑ ምስክርነታቸውን በአማራኛ እና በእንግሊዘኛ ቋንቋዎች የሚሰጡ ሰዎች ስታይ በይበልጥ ጉጉት አደረባት። 10,000 ብር ኢንቨስት ስታደርጊ 180,000 ብር ትርፍ እናከፋፍላለን የሚሉ ማባበያዎችን እንዲ በቀላሉ ማለፍ አልቻለችም ነበር። ቴሌግራም ላይ ያለ ኤጀንት መጀመሪያ በትንሹ ጀምራ ከዛ እያሳደገች እንድትሄድ እና እንዴት
እንደሚሰሩ እንድታይ ምክረ-ሀሳብ ያቀርብላታል። ከዛም ወ/ሪት ሄለን ገንዘቡን አስገብታ ቃል የተገባላት ገንዘብ ከ 24 ሰዓት በኋላ ይገባላታል። ይህ ድርጊት ወ/ሪት ሄለንን በጣም ያስደሰተ እና ከሌሎች ሰዎች ተበድራም ቢሆን ኢንቨስት በማድረግ ትርፏን ማሳደግ እና ብድሮቿን ቶሎ መመለስ እንደምትችል በማመን በተለያዩ ሰዎች ስም ከፍ ያለ ገንዘብ ኢንቨስት ታደርጋለች። የምታገኘው ተመላሽ ገንዘብ ከፍ ማለቱን ተከተሎ ትላንት አምናቸው ኢንቨስት ያደረገችባቸው ተቋም ደብዛቸውን አጥፍተው ባዶ እጇን ሲያስቀራት ነበር የደረሰባትን ማመን ያቃታት። ወ/ሪት ሄለን በአጠቃላይ ከ 390ሺህ ብር በላይ በአጭበርባሪዎች አጥታለች።
ጥቃት አድራሾች ወ/ርት ሄለንን ለማታለል የተጠቀሙበት ዘዴ ምን ነበር?
ጥቃት አድራሾች ሄለንን ለማታለል የተጠቀሙበት ቴክኒክ ኢንቨስትመንት ማጭበርበር (Investment Scams) የሚባለውን ሲሆን ይህም የሰዎችን ልምድ አለመኖር እና ፍራቻን በማጫር የሚፈፅም የማታለል ዘዴ ነው።
በክፍል ሁለት ቀጣይ ሳምንት ስለ ኢንቨስትመንት ማጭበርበር (Investment Scams) ምንነት፣ ባህሪያት እና መከላከያ መንገዶችን የምንጠቁማችሁ ይሆናል።
በምንለቃቸው የደህንነት ምክረ-ሀሳቦች ላይ ተመሳሳይ ታሪክ፣ ሀሳብ እና አስተያየት ካሎት በ t ያጋሩን ስንል በትህትና እንጠይቃለን።