27/07/2026
"ሞቴን አየሁ በሕልሜ።"
መንቀሳቀስ አልችልም፤ መናገርም አልችልም። ከሰው ጓሮ ወድቄ፣ በጥልቅ ጨለማ ውስጥ ለቀናት ተጋድሜ እቀራለሁ።
በመጀመሪያው ቀን ነፍሴ ልትነሳ ፈለገች፤ ግን አልቻለችም። ድብልቅልቅ ያለ ድምፅ እሰማለሁ፤ መናገር እፈልጋለሁ፣ ግን ድምፅ አይወጣም።
"አነሳለሁ" ማለት እፈልጋለሁ፤ ነገር ግን "ሞቻለሁ" የሚል እውነት ፊቴን ይመታኛል። ልቤ አይቀበለውም፤ ግን እውነታው አይቀየርም።
በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ማንም የማያየኝ፣ የማላውቀው አውሬ በዙሪያዬ ሲያንዣብብ እሰማለሁ። አይኔ አይከፈትም፤ አንገቴ አትቀናም። "ሂድ... ሂድ..." የሚል ድምፅ ከውስጤ ይገፋፋኛል፤ እኔ ግን ምንም ማድረግ አልችልም።
ቀናት አለፉ። በሦስተኛው ቀን ሰውን ማየት ብቻ ሳይሆን፣ የእናቴን ድምፅ መስማት ምኞቴ ሆነ። መጮህ ፈለግሁ፤ ግን ድምፅ አልወጣም። በዚያ ቀን ሰውነቴ እንደከዳኝ ተሰማኝ።
አንድ ምሽት የጎረቤት ድምፅ ጆሮዬን ነካ። በቀረው ኃይሌ "እዚህ ነኝ... ከጓሮ ጀርባ..." ለማለት ሞከርሁ፤ ግን የወጣው ድምፅ ለእኔም እንኳ አልተሰማኝም።
ተስፋ ቀስ በቀስ ጠፋ። ከዚያ በኋላ ስለ ሕይወት ሳይሆን ስለ መቀበር ማሰብ ጀመርሁ። ከአያቴ ጎን ብቀበር ብዬ ተመኘሁ፤ ያ ምኞት ብቻ ፈገግታን አመጣልኝ።
ከግማሽ ሌሊት በኋላ አንድ እውነተኛ ድምፅ ሰማሁ። ግን ያኔ በጣም ዘግይተው ነበር። ነፍሴ ወጥታ ነበር። ሊያድኑኝ አልቻሉም፤ ግን የሚያውቁኝ ዘመዶቼ አስከሬኔን አገኙት።
በዚያ ጊዜ አንድ ምኞት ብቻ ቀረልኝ፤ እናቴን ማግኘት። ማቀፍ ባልችልም፣ ማናገር ባልችልም፣ ቢያንስ አስከሬኔ እሷ ዘንድ ይድረስ ብዬ ፈጣሪን ለመንሁ።
እርሱም ምኞቴን አልነፈገኝም።
እየተሸከሙ ወደ እናቴ አደረሱኝ። አይኖቼ ማየት ባይችሉም፣ ጠረኗን አሸተትሁ፤ ድምጿንም ሰማሁ።
ያን ጊዜ የተሰማኝን ደስታ በቃላት መግለጽ አልችልም። እንባዬ ገደብ አላወቀም፤ እንደ ሕፃን ልጅ አለቀስሁ።
እሷም "ልጄ... ልጄ..." እያለች አቀፈችኝ። በስሜ እየጠራች፣ "አይ ልጄ... እንዴት እንዲህ ሆንክ?" ብላ አለቀሰች።
የእንባዬን መልስ እንደተረዳች፣ "አይዞህ... አይዞህ..." እያለች አጽናናችኝ።
እኔም የመጨረሻ ኃይሌን ሰብስቤ ቀስ ብዬ እንዲህ አልኳት፦
"እናቴ... ከአያቴ ጎን እንድቀበር አድርጊልኝ።"
ቃሉን ከተናገርኩ በኋላ የምመኘው ነገር አልቀረም። የሞት ፍርሃትም ሆነ የሕይወት ምኞት በአንድ ላይ ጸጥ አሉ።
በዚያ ቅጽበት አንድ እውነት ብቻ ገባኝ፤
ሰው በመጨረሻ የሚፈልገው ሀብት ወይም ዝና አይደለም፤ የሚወደው ሰው እቅፍ ነው።
ከእናቴ እቅፍ ውስጥ ያለውን ሙቀት እየተሰማኝ፣ እንባዬ ቀስ በቀስ ረገበ፤ ሕልሙም በጨለማ ውስጥ ቀስ ብሎ ተሟሟ።
💔💔
ሐምሌ, 20, 2018, @ 12:10 ስዓት