13/04/2022
ህወሓት ከአፋር ክልል ኤሬብቲ አካባቢ ተዋጊዎቼን አስወጥቻለሁ አለ !
ከፌደራል መንግሥቱ ጋር ጦርነት ውስጥ የገባው ህወሓት በአፋር ክልል ኤሬብቲ ተብሎ የሚጠራ ስፍራን ተቆጣጥረው የነበሩ ተዋጊዎቼ አካባቢውን ለቅቀው እንዲወጡ አድርጊያለሁ አለ።
ህወሓት ሠራዊቱን ኤሬብቲ ተብሎ ከሚጠራው ስፍራ ለማስወጣት ከውሳኔ የደረሰው ለሰብአዊነት ሲባል የተደረሰው ስምምነት ተከብሮ ያልተገደብ ሰብአዊ እርዳት ትግራይ እንዲደርስ ነው ብሏል።
ዛሬ ሚያዚያ 5/2014 ዓ.ም. በክልሉ ቴሌቪዥን ጣቢያ በተላለፈው መግለጫ፤ "የትግራይ መንግሥት የሰላም ውይይቱን ለማሳለጥ በተለይም ለሰብአዊ እርዳታ አቅርቦት ሚያዚያ 4/2014 ዓ. ም. የትግራይ ሠራዊት ተቆጣጥሮት ከነበረው ኤሬብቲ ተብሎ ከሚጠራው የአፋር አካባቢ ሠራዊቱ እንዲነሳ ተደርጓል" ብሏል።
ህወሓት ይዟቸው ከነበራቸው የአፋር ክልል አካባቢዎች ለቅቆ ስለመውጣቱ ከአፋር ክልል መንግሥት ለማረጋገጥ ያደረግነው ጥረት ስልክ ባለመሳነቱ ሳይሳካ ቀርቷል። የህወሓት ኃይሎች በአፋር ክልል ዞን ሁለት የሚገኙ ወረዳዎችን በቁጥጥራቸው ስር ያዋሉት በጥር ወር አጋማሽ ላይ ነበር።
ምንጭ፦ BBC